የዳንኤል መጽሐፍ በባቢሎን ምርኮ እና በመቀጠል በፋርስ አገዛዝ ጊዜ የተከናወኑ ታሪኮችን፣ ትንቢቶችን እና “የፍጻሜ ዘመን” ራእዮችን ያጣመረ እጅግ ማራኪ መጽሐፍ ነው። መጽሐፉ በዋናነት በሁለት ክፍሎች የተከፈለ ነው። የመጀመሪያዎቹ ስድስት ምዕራፎች (1-6) የዳንኤልን እና የሶስቱ ጓደኞቹን— ሐናንያን፣ ሚሳኤልንና አዛርያን (ሲድራቅ፣ ሚሳቅና አብደናጎ)—ታሪክ ይዘዋል። እነዚህ ታሪኮች በባቢሎን ቤተ መንግሥት ውስጥ ከፍተኛ ጫና እና ስደት ቢደርስባቸውም ለእግዚአብሔር ያላቸውን ታማኝነት እና ጽናት ያሳያሉ። ታሪኮቹ ሦስቱ ጓደኛሞች በእቶን እሳት ውስጥ መትረፋቸውን፣ ዳንኤል የንጉሥ ናቡከደነፆርን ትንቢታዊ ሕልሞች መተርጎሙን፣ ግድግዳው ላይ የተጻፈውን ምስጢራዊ ጽሑፍ፣ እና ዳንኤል ከአንበሶች ጉድጓ ድ መዳኑን የመሰሉ ታላላቅ ክስተቶችን ያካትታሉ። እነዚህ ታሪኮች ለምርኮኝቹ አይሁዳውያን እግዚአብሔር ሉዓላዊ መሆኑንና በእርሱ የሚታመኑትን እንደሚያድን ለማበረታታት ያገለግላሉ።
የመጽሐፉ ሁለተኛ አጋማሽ (ምዕራፎች 7-12) በአጻጻፍ ስልት እና በይዘት በእጅጉ ይለያያል። በዚህ ክፍል ውስጥ ዳንኤል ስለ ዓለም የወደፊት ሁኔታ እና የእግዚአብሔር ሕዝብ የሚቀበላቸውን የፍጻሜ ዘመን ራእዮች ያሳያሉ። እነዚህ ራእዮች እጅግ ምሳሌያዊ ቋንቋን በመጠቀም፣ አራት ተከታታይ የዓለም ነገሥታትን የሚወክሉ አስደናቂ አራዊትን (ባቢሎን፣ ሜዶን-ፋርስ፣ ግሪክ እና ሮምን/ወይም የመጨረሻውን መንግሥት) ያሳያሉ፤ መጨረሻ ላይም “የሰው ልጅ የሚመስል” (ዳንኤል 7:13) በሚገዛው ዘላለማዊ መንግሥት መመስረት ይጠናቀቃል። ይህ ክፍል እንደ “ሰባው ሳምንታት” (ዳንኤል 9) ያሉ ውስብስብ የዘመን ቅደም ተከተል ትንቢቶችን ያቀርባል፤ ይህም የመሲሑን መምጣት እና ከዚያ በኋላ የሚከሰቱትን ክስተቶች ዝርዝር የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል።
በራእዮች ሁሉ ውስጥ ዋነኛው ነገረ-መለኮታዊ ጭብጥ የእግዚአብሔር ሉዓላዊነት በሁሉም የሰው ልጅ ታሪክ ላይ የሚለው ነው። ዳንኤል ምድራዊ መንግሥታት በተከታታይ ቢነሱና ቢወድቁም ኃይላቸው ጊዜያዊ መሆኑንና በመጨረሻም “ከሁሉ በላይ በሆነው” ሥር መገዛታቸውን ያሳያል። መጽሐፉ እንደ ናቡከደነፆር እና ብልጣሶር ያሉ ነገሥታት ያለባቸውን ትዕቢትና ጊዜያዊ ሥልጣን በእግዚአብሔር ዘላለማዊ ግዛት እና ኃይል ጋር ያነጻጽራል። እግዚአብሔር ለታሪክ ግልጽና አስቀድሞ የተወሰነ ዕቅድ እንዳለው ያጎላል፤ ይህም የሕዝቡን መከራ እና የመጨረሻ ማረጋገጫ/መዳን፣ በጻድቃን ትንሣኤ (ዳንኤል 12:2) እና በኃጢአተኞች ፍርድ ያጠናቅቃል።
የመጨረሻዎቹ ምዕራፎች (10-12) ከታላቁ እስክንድ ሞት በኋላ በሄለናዊ መንግሥታት (“የሰሜን ንጉሥ” እና “የደቡብ ንጉሥ” - በተለይም የሴሉከስ እና የትሎሚ ግዛቶች) መካከል ስላለው ትግል የሚያተኩር ዝርዝር ትንቢት ይዟል። ይህ ክፍል በይበልጥ ደግሞ በቤተ መቅደሱ ላይ ረብሻ ያደረሰውን እና አይሁዳውያንን ያሳደደውን አራተኛው አንቲዮከስ ኤጲፋንስን (በምዕራፍ 8 ላይ ያለው “ታናሹ ቀንድ”) ግፍ በዝርዝር ይገልጻል። ምንም እንኳን ይህ ትንቢት በ2ኛው ክፍለ ዘመን ከክርስቶስ ልደት በፊት ግልጽ ፍጻሜ ቢኖረውም፣ የመከራ እና የመዳን ጭብጦቹ “በመጨረሻው ዘመን” ለሚመጡት ታላላቅ መከራዎች ቅድመ እይታ እንደሆነ በብዙዎች ይታያል።
በማጠቃለያው፣ የዳንኤል መጽሐፍ በችግር እና በፖለቲካዊ ውዥንብር ጊዜያት ውስጥ ላሉ የእግዚአብሔር ሕዝብ ተስፋንና ጽናትን - HOPE and ENDURANCE ለመስጠት የታሰበ ጥልቅ ነገረ-መለኮታዊ መግለጫ ነው። ምንም እንኳን ጨቋኝ ምድራዊ ኃይሎች ቢኖሩም፣ የዘመናት አካሄድ በእግዚአብሔር ውሳኔ የተስተካከለ መሆኑን ያረጋግጣል፤ ይህም የጽድቅ ማበብን እና የዘላለማዊ መንግሥቱን መመስረት አይቀሬነት የሚያሳይ ነው። በመጨረሻም፣ ለሞት በሚዳርግ ሁኔታ ውስጥ ታማኝነት በአምላካዊ ድነት እና በዘላለም ሕይወት እንደሚካስ በማረጋገጥ፣ ለአማኞች የእምነት ጥሪ ሆኖ ያገለግላል።
ይህን ዓይነተኛ መጽሐፍ ስናስብ ምን እናስብ?
#አንድ፤
እግዚአብሔር በመንግሥታት ሁሉ ላይ ሉዓላዊ ነው፡
ዋናው መልእክት ራሱን የእስራኤል አምላክ በማለት የገለጸው እውነተኛውና ሕያው አምላክ የዓለም ሁሉ ፍጹም ገዥ መሆኑ ነው። በአራቱ መንግሥታት ተተካኪነት የተወከለው ምድራዊ ኃይል ሁሉ ጊዜያዊ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ለፈቃዱም ተገዢ ነው። ለናቡከደናጾር “ልዑል በሰው ነገሥታት ላይ ገዥ እንደ ሆነ፥ ለወደደውም እንዲሰጠው ታውቅ ዘንድ ይገባሃል” (ዳንኤል 4:25$) እንደተባለው መንግሥት እና ሥልጣን የእግዚአብሔር እንጂ የሰው አለመሆኑን መረዳት ይቻላል፡ እግዚአብሔር የላዕላይ ባለሥልጣን ነው - He remains the ultimate authority over all things.
#ሁለት፤
በስደት እና በመከራ መካከል ያለ ታማኝነት፡
የዳንኤል መጽሐፍ የታሪክ ትረካዎች ለአንድ አምላክ የሚደረግ ጽኑ ታማኝነትን ያጎላሉ። ዳንኤል እና ጓደኞቹ በሞት ዛቻ (በእሳት እቶን፣ በአንበሶች ጉድጓድ) ፊት የማይበገር ድፍረትንና ታማኝነትን በማሳየት፣ ለአንዱ እግዚአብሔር ያለው ቁርጠኝነት ከማንኛውም ሰብአዊ ሥልጣን በላይ መሆን እንዳለበት ይጠቁማሉ፡ ምንም እንኳን ከአባቶቻቸው የተስፋ ምድር ርቀው ቢነጉዱም፣ ምንም እንኳን ቤተመቅደሱ ቢቃጠልና በባዕድ ምድር ዋጋቸውን ቢያጡ ኢየሩሳሌምን ግን አይረሷትም ነበር፡ ከኢየሩሳሌም ወጥተው እንኳን ኢየሩሳሌም ከልባቸው አትወጣም ነበር፣ ስለዚህም በመከራቸውና በስደታቸው ለአባቶቻቸው አምላክ ያልተዳቀለ ታማኝነትን እና አምልኮን በመስጠት ቀጥለው ነበር - ባያድናቸውም እንኳን።
#ሦስት፤
የዘላለም መንግሥት ዋስትና፡
የፍጻሜው ዘመን ራእዮች የመጨረሻውን ተስፋ ይፈነጥቃሉ፡ “በሰው ልጅ” የሚገዛ የወደፊት መንግሥት ሁሉንም የተበላሹ ምድራዊ ግዛቶችን አጥፍቶ የጽድቅ ዘላለማዊ ግዛትን እንደሚመሰረት ያበስራሉ፡ ይህ አዲስ መንገሥት ደግሞ በመጨረሻ ትንሣኤ እና መለኮታዊ ፍርድ የሚገለጥበት የእግዚአብሔር ሉአላዊ አሰራር እንደሆነም ይመሰክራሉ፡ የአሮጌው ስርአት መጋረጃ ይቀደድና የአዲሱ ዘመን ወይም ስርአት መጋረጃ ሲከፈት እግዚአብሔር ራሱ የታሪክ ባለቤት፣ ተቆጣጣሪና፣ ፈጻሚ መሆኑን እናስተውላለን - በስተመጨረሻ እግዚአብሔር ራሱ ታሪክን በመሰብሰብና እልባት በማስያዝ “the unmoved mover” መሆኑን በገሃድ ያስመሰክራል።
#ጭማቂ፤
የእግዚአብሔርን ሉአላዊነት በማሰብ፣ በታማኝነት እና በጽናት የዘላለምን መንግሥት ዋስትና እና ተስፋ አጥብቀን እንይዛለን።
#ጸሎት፤
በትእቢት እና በማን አለብኝነት ልባችን ተሞልቶ በጌታ ከተሰጠን ከአገልግሎት ሰገነት ላይ ተጥለን እና ጸጋ ርቆን ሳር ከመብላት ያድነን - ልብሰ ንግሥናው (ክህነቱ) ተገፍፎበት ነገር ግን አሁንም ንጉሥ (ካህን) እንደሆነ ሰው ከማሰብና ፐርፎርም ከማድረግ ያድነን: እንደ ናቡከደናጾር ሳይረዝምብን ቶሎ እንድንነቃ ይርዳን::
















































































